የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር በቦሌ ክፍለ ከተማ ከ1 ቢሊየን ብር በላይ በሆነ ወጪ ያስገነባቸው 65 ፕሮጀክቶች በዛሬው እለት ተመርቀው ለአገልግሎት ክፍት ሆነዋል።

ከተመረቁት ፕሮጀክቶች መካከል 41 በከተማ አስተዳደሩ በጀት የተገነቡ 2015 የበጀት ዓመት የካፒታል ፕሮጀክቶች ሲሆኑ 24 ደግሞ በህብረተሰብ ተሳትፎ የተገነቡ ፕሮጀክቶች ናቸው።

ፕሮጀክቶቹን መርቀው ስራ ያስጀመሩት የአዲስ አበባ ከተማ ምክትል ከንቲባ እና የስራ ኢንተርፕራይዝ እና ኢንዱስትሪ ልማት ቢሮ ኃላፊ አቶ ጃንጥራር አባይ 2015 የበጀት አመት የከተማ አስተዳደሩ 60 በመቶ የሚሆነውን የከተማዋን በጀት ለካፒታል ፕሮጀክቶች በመመደብ እና የከተማውን ህዝብና ባለሀብት በማስተባበር ህዝብን ተጠቃሚ የሚያደርጉ ፕሮጀክቶችን ገንብቶ በማጠናቀቅ ለህዝብ ተጠቃሚነት እያዋለ ነው ብለዋል።

የከተማ አስተዳደሩ ልዩ ትኩረት የሰጣቸው የትምህርት የጤና ተቋማት፣ የመንገድ እና የውሃ ፕሮጀክቶች ግንባታ ስራዎች የህብረተሰቡን ተጠቃሚነት ለማረጋገጥ በከፍተኛ ርብርብ እየተሰሩ መሆናቸውን አቶ ጃንጥራር ተናግረዋል።

የተገነቡ ፕሮጀክቶች በዘላቂነት አገልግሎት መስጠት እንዲችሉ ህብረተሰቡ አስፈላጊውን ጥበቃ እና እንክብካቤ እንዲያደርግም አቶ ጃንጥራር ጥሪ አቅርበዋል።

በፕሮጀክት ግንባታው ሂደት 1 900 በላይ ለሚሆኑ ዜጎች የስራ እድል መፍጠር የተቻለ ሲሆን፣ በህዝብ ተሳትፎ ለተሰሩ ፕሮጀክቶች 500 ሚሊየን ብር በላይ የሆነ ሀብት ማሰባሰብ መቻሉን እና ለካፒታል ፕሮጀክቶችም እንዲሁ 500 ሚሊየን ብር በላይ በጀት ተመድቦ ፕሮጀክቶቹ መገንባታቸውን የቦሌ ክፍለ ከተማ ዋና ስራ አስፈጻሚ ወይዘሮ አለምጸሀይ ሽፈራው ተናግረዋል።

ከተመረቁ ፕሮጀክቶች መካከል የጤና ጣቢያዎች ማስፋፊያ ትምህርት ቤቶች የፖሊስ ጣቢያዎች የውስጥ ለውስጥ መንገዶች የአረንጓዴ ስፍራዎች የወረዳ ማዕከላትን ለስራ ምቹ እና ውብ የማድረግ ዝቅተኛ ገቢ ያላቸውን ዜጎች ተጠቃሚ የሚያደርግ የመኖሪያ ቤት ግንባታ ፕሮጀክቶች የህጻናት እና ወጣቶች የስፖርት ማዘውተሪያ ስፍራዎች ይገኙባቸዋል።

Share this Post