26
Jul
2021
በአዲስ አበባ ከተማ ለመከላከያ ሰራዊታችን የሚደረገው ድጋፍ ዛሬም በተለያዩ ክፍለ ከተሞች ተጠናክሮ ቀጥሏል። በልደታ፣በቦሌ፣በአራዳ ፣በንፋስ ስልክ ላፍቶ ፣የካየካ፣ጉለሌ እና በአዲስ ከተማ ክፍለ ከተሞች ነዋሪዎች ለጀግናው መከላከያ ሰራዊታችን ደጀንነታቸውን ለማሳየት የገንዘብ ፣የተለያዩ ቁሳቁሶች እና የሰንጋ እና የበግ ድጋፍ አድርገዋል። የልደታ ክፍለ ከተማ ነዋሪዎች፣ ባለሀብቶችና አመራሮች ለመከላከያ ሰራዊት ድጋፍ የጥሬ ገንዘብ፣ የምግብ ቁሳቁስና 200 በጎችን በጠቅላላው ከ12.5 ሚሊየን ብር በላይ የሚገመት ድጋፍ ተደርጓል ። በቦሌ ክፍለ ከተማ እስከ ወረዳ ድረስ የሚገኙ አጠቃላይ አመራሮች 685 በጎች እና ፍየሎችን፣ ሴት አደረጃጀቶች 70ኩንታል በሶ፣ 5 ኩንታል ዳቦ ቆሎ፣3 በሬዎች እንዲሁም የተለያዩ የምግብ ቁሳቁሶች በአጠቃላይ ከ15.5 ሚሊዮን ብር በላይ የሚገመት ለሀገር መከላከያ ሠራዊት ድጋፍ አድርገዋል። በአራዳ ክፍለ ከተማ የሚገኙ ነዋሪዎችም ለሀገር መከላከያ ሰራዊት አብሮነታቸውንና የኋላ ደጀንነታቸውን ለማሳየት ከ301 በጎችና 18 በሬዎች እንዲሁም የተለያዩ የምግብ ቁሳቁሶች በጠቅላላው ከ 15 ሚሊዮን ብር በላይ ድጋፍ አድርገዋል ። በንፋስ ስልክ ላፍቶ ክፍለ ከተማ የሚገኙ ነዋሪዎችም በተመሳሳይ ለሀገር መከላከያ ሰራዊት ደጀንነታቸውን ለማሳየት ሰንጋ በሬዎች ፣በጎች እና የተለያዩ የምግብ ቁሳቁሶች በጠቅላላው ከ40 ሚሊዮን ብር በላይ ድጋፍ አድርገዋል ። የየካ ክፍለ ከተማ አስተዳደርም ለመከላከያ ሰራዊት የሚሆን ከ17ሚሊዮን ብር በላይ የሚገመት በገንብና በዓይነት ፣የደረቅ ምግብ እና ሌሎች ቁሳቁሶች ድጋፍ አሰባስቧል ። የጉለሌ ክፍለ ከተማ አስተዳደር ለጀግናው የመከላከያ ሰራዊት ከነዋሪዎችና ባለሃብቶችን በማስተባበር የደረቅ ምግብና የንጽህና መጠበቂያ ቁሳቁስ፣20 ሰንጋዎችን ፣ 581 በጎችና ፍየሎችን እንዲሁም ከ6 ሚሊዮን ብር በላይ በጥሬ ገንዘብ በጠቅላላው ከ20 ሚሊዮን ብር በላይ ማሰባሰብ ተችሏል ። በተያያዘም በአዲስ ከተማ ክፍለ ከተማ ባለሀብቶችን እና ነዋሪዎችን በማስተባበር ከ9 ሚሊዮን ብር በላይ የሚገመት የጥሬ ገንዘብ እና የተለያዩ የምግብ አይነቶችን ድጋፍ ተደረጓል ። በቀሪዎቹ ክፍለ ከተሞችን በተመሳሳይ ለሰራዊቱ ድጋፍ እየተሰበሰበ ይገኛል ተብሏል ።