"ኢትዮጵያ አንድነት ዘብ እቆማለሁ" በሚል ከአዲስ አበባ ከተማ እና ከኦሮሚያ ፊንፊኔ ዙሪያ ልዩ ዞን ከተሞች የተውጣጡ በርካታ ነዋሪዎች የሀገር መከላከያ ሰራዊትን ለመደገፍ እና የህወሓት የጥፋት ቡድንን ለማውገዝ በመስቀል አደባባይ ሰላማዊ ሰልፍ አካሂደዋል ።
በሰላማዊ ሰልፉ ምክትል ከንቲባ ወ/ሮ አዳነች አቤቤ ባደረጉት ንግግር ሰላም በአንድ ወገን ብቻ ሊገኝ የሚችል አማራጭ አይደለም ያሉ ሲሆን ዛሬ የምናሰማው ድምጽ የጁንታው የተንኮል እና የሴራ ተግባር የሚቃወም ድምጽ ነው፤ እስከ ሕይዎት መስዕዋትነት የምንከፍልበት ድምጻችን ነው ብለዋል፡፡
ኢትዮጵያን የሚመራት ኢትዮጵያውያን የመረጡት መሪ እንጂ፤ ሌሎች የሚያስቀምጡልን አሻንጉሊት መንግስት አይደለም ያሉት ምክትል ከንቲባዋ ኢትዮጵያን የሚመራት ኢትዮጵያውያን ሁሉንም ተጽዕኖ ተቋቁመው የመረጡት መንግስት ብቻ እንደሆነም ገልጸዋል።የመከላከያ ሰራዊታችንና መላው የጸጥታ ሃይላችን ለኢትዮጵያ ክብር ተመን የማይገኝለት ዋጋ እየከፈለ መሆኑን የገለጹት ወ/ሮ አዳነች አቤቤ ለዚህመ ታላቅ ክብር ይገባቸዋል፣ እንደግፋቸዋለን፣ አብረናቸውም እንቆማለን ብለዋል ።እኛ ኢትዮጵያዊያን ማንኛውንም መስዋዕትነት ለመክፈል የተዘጋጀን ህዝቦች ነን ያሉት ምክትል ከንቲባ አዳነች አቤቤ፤ የኢትዮጵያ ጀግንነት ተጠናክሮ ይቀጥላል፤ አንድነቷም ከብረት ይጠነክራል ብለዋል ።
100 ሚሊየን ህዝብ ሊደመጥ ይገባል ያሉት ምክትል ከንቲባ ወ/ሮ አዳነች አቤቤ ሌሎች አካላት ኢትዮጵያውያን የቀበሩትን አሸባሪውን የህወሓት ጁንታ ቡድን ከሞተበት ለማስነሳት የሚያደርጉትን ሙከራ እንዲቆምም ጥሪ አቅርበዋል፡፡የኦሮሚያ ክልል ርዕሰ መስተዳድር አቶ ሽመልስ አብዲሳ በበኩላቸው ጁናታው ወጣቶቻችን በስናይፐር ገድሎብናል፤ ዘርፎናል፤ ከፋፍሎናል በመሆኑም ይህን ተግባሩን ዳግም በኢትዮጵያውያን ላይ እንዲፈጽም አንፈቅድለትም ብለዋል።ጁንታው በመቶ ሰዎች ወንበር ላይ ብቻውን ሲቀመጥ እና እንደፈለገው ሲያዝ ነበር ያሉት አቶ ሺመልስ አብዲሳ አሁን የሁሉም ኢትዮጵያዊያን ብሄር ብሄረሰብ ወንበር እንዲሆን መደረጉን ገልጸዋል፡፡
መላው ኢትዮጵያዊያን በአንድ በኩል ልማት በሌላ በኩል ደግሞ አሸባሪውን የህውሃት ጁንታ ለመመከት ሁሉም ሊረባረብ እንደሚገባ የገለፁት አቶ ሽመልስ አብዲሳ ኢትዮጵያዊያነት ደማችን ውስጥ ያለ በመሆኑ ማንም ሊበትነን እና ሊለያየን አይችልም ብለዋል ።