ኢትዮጵያ የአፍሪካ ቀንድ ላይ የምትገኝ አንዲት ሀገር ብቻ አይደለችም። ኢትዮጵያ መላው ዓለም ነች። በቀድሞው ዘመን እንግሊዛውያን የቅኝ ግዛታቸውን ሥፋት ለማሞካሸት የሚጠቀሙበት አገላለፅ፣ የአሁኑን ኢትዮጵያን ትክክለኛ ግዝፈትና ዓለምአቀፋዊነት ያሳያል። «በኢትዮጵያ ግዛት ላይ ፀሐይ አትጠልቅም!» ። ለምን ቢሉ ኢትዮጵያውያን ባሉበት ሁሉ ኢትዮጵያ በዚያ አለች።
ጠቅላይ ሚኒስትር ዐብይ አህመድ በመጀመሪያው የጠቅላይ ሚኒስትር ሹመት ንግግራቸው እንዳሉት...
«እያንዳንዱ ኢትዮጵያዊ ለሥራም ሆነ ለትምሕርት በሄደበት ሁሉ ኢትዮጵያን ተሸክሟት ይዞራል። ኢትዮጵያዊን ከኢትዮጵያ ታወጡት እንደሆነ እንጂ ኦትዮጵያን ከኢትዮጵያዊ ልብ ውስጥ አታወጧትም የሚባለው ለዚህ ነው።»
በዓለም ዙሪያ ያሉ ኢትዮጵያውያን በቅብብል የኢትዮጵያ እውነት ላይ ፀሐይ እንዳይጠልቅበት በዓለም አደባባይ ለሀገራቸው እንደራሴነታቸውን በተግባር እያስመሰከሩ ነው። እውነታችንን ያፈኑትንና ረጅም እጃቸውን ወደ ውስጣዊ ጉዳያችን ያስገቡትን አንዳንድ የምዕራባዊ መንግስታትና ሚዲያዎች እያፋጠጡና እየተቹ ነው። ኢትዮጵያ መሬት ላይ ያለውን እውነታ በፍፁም ኢትዮጵያዊ ክብርና ጨዋነት እያስተጋቡ ነው።
በዩ.ኤስ አሜሪካ በብዙ ግዛቶች፣ በካናዳ፣ በእንግሊዝ፣ በፈረንሳይ፣ በጀርመን፣በጣሊያን፣በስዊድን በግሪክና በብዙ የአውሮጳ ሀገራት፤በጃማይካ፣ በደቡብ አፍሪካ፣ በሊባኖስ፣ በአውስትራሊያና በብዙ የዓለም ሀገራት ኢትዮጵያንና የኢትዮጵያ ወዳጆች የመላው ኢትዮጵያዊን ልብ የሚያሞቅ የዲፕሎማሲ ተጋድሎ ፈፅመዋል።በጣም በአጭር ጊዜ ውስጥም ከፍተኛ ቁጥር ያለው ገንዘብ በማሰባሰብ ወደሀገራቸው በመላክ የኢትዮጵያ ደጀንነታቸውን እያስመሰከሩ ይገኛሉ። ከዚህ በፊት ምንም አይነት ሰልፍም ሆነ የፖለቲካ እንቅስቃሴ ላይ ተሳትፈው የማያውቁ ሁሉ በታላቅ ሀገራዊ ስሜት የ#Nomore ዘመቻው ላይ እየተሳተፉ ይገኛሉ። በቅርቡ ደግሞ የኢትዮጵያን ሰላማዊነት ለዓለም የማሳየት ያለመውን የጠቅላይ ሚኒስትር ዐብይ አህመድን የ«ወደሀገር ቤት ግቡ» ጥሪ ተቀብለው ብዙዎቹ ወደሀገራቸው ሊገቡ እየተዘገጃጁ ነው። ኢትዮጵያ በሁሉም ግንባር ስለባንዲራዋና ክብሯ የሚዋደቁትን ሁሉ ታመሰግናለች።