የመረጃ አያያዝ ስርዓት በማዘመን ህገ ወጥነትን መከላከል ይገባል

 

ለከተማ ቤቶች አስተዳደር ስርዓት የሚያገለግል ሶፍት ዌር በከተማና መሰረተ ልማት ሚኒስቴር የቤቶች ልማትና አስተዳደር ቢሮ ለምቶ በይፋ የስራ ማስጀመሪያ ፕሮግራም ተካሂዷል፡፡

በፕሮግራሙ ላይ ንግግር ያደረጉት ከንቲባ አዳነች አቤቤ የለዉጡ አመራር ወደ ስራ ሲገባ ተግባራዊ ሊያደርጋቸዉ ቃል ከገባባቸዉ ጉዳዮች መካከል አንዱ አሰራሮችን ቀልጣፋ ፤ ግልፅ ማድረግ በመሆኑ የመረጃ አያያዝ ስርዓትን ለማዘመን ዛሬ ተግባራዊ የሆነው ሶፍትዌር አንዱ መሆኑን አንስተዋል።

ህብረተሰቡ የሚፈልገውን አገልግሎት በአግባቡ ለመስጠት ሶፍት ዌሩ ላይ የሚገቡ መረጃዎችን ከመሰብሰብ ጀምሮ አጠቃላይ ተግባራዊነቱ ላይ ትኩረት በመስጠት ሊሰራበት ይገባል ብለዋል፡፡

ፍትሃዊነትን ለማስፈንና ብልሹ አሰራርን ለመከላከል ለትክክለኛ መረጃ አያያዝ የሚያገለግሉ ሶፍትዌሮችን መጠቀም ጥቅሙ የጎላ እንደሆነ ገልፀዋል።

የከተማ አስተዳደሩ በከተማዉ የሚገኙ ቤቶችን በዚህ ዘመናዊ የመረጃ አያያዝ ሶፍትዌር አማካኝነት በማስተዳደር ሌብነትና ህገ ወጥነት እንዳይስፋፋ ይሰራል ብለዋል፡፡

ሶፍት ዌሩ የቀበሌ ቤቶች ኮንደምንየሞች፤ ማህበራት ቤቶች፤ ህንፃዎች፤ ክፍት ቦታዎች ያሉበትን ቦታ በመመዝገብ በመረጃ ስለሚይዝ የፋይል መጥፋትና መሰል ችግሮችን ይቀርፋል ተብሏል፡፡

Share this Post