የአዲስ አበባ ከተማ ምክር ቤት ለ2014 በጀት ዓመት 70 ቢሊዮን 670 ሚሊዮን ብር አጽደቀ።

የአዲስ አበባ ከተማ ምክር ቤት 8ኛው ዓመት የስራ ዘመን 3ኛ መደበኛ እና የስራ ዘመን ማጠቃለያ ጉባኤ ከጠዋት ጀምሮ በፌዴሬሽን ምክር ቤት አዳራሽ ሲያካሂድ የነበረውን ጉባኤ ለ2014 በጀት ዓመት 70 ቢሊዮን , 670 ሚሊዮን ,216 ሺህ ,028.31 ብር በጀት በሙሉ ድምጽ በማጽደቅ ማምሻውን ተጠናቋል ።

ለ2014 በጀት ዓመት የተመደበው በጀት ለካፒታል እና መደበኛ ስራዎችን ትኩረት በመስጠት የከተማዋን የኢኮኖሚ ዕድገት ማስቀጠል እና የነዋሪዎችን ፍትሃዊ ተጠቃሚነት ይበልጥ ማረጋገጥ በሚያችል መልኩ መደልደሉን የከተማ አስተዳደሩ የፋይናንስ ቢሮ ኃላፊ ወ/ሮ ነጂባ አክመል ተናግረዋል ።

በተጨማሪም የቀጣይ 10 ዓመት እና 5 ዓመት መሪ ዕቅድን የተመለከቱ የትኩረት አቅጣጫዎችንና ስትራቴጂክ ግቦችን መሰረት ባደረገ መልኩ በተለይ ለቤቶች ልማትና ኮንስትራክሽን ፣ ለውሃና ፍሳሽ ፣ለጤና ፣ ለትምህርትና ስልጠና ፣ ለመንገድ እና ለትራንስፖርት ፣ የአረንጓዴ ልማት እና እድገት ተኮር በሆኑ ዘርፎች መሆኑን ኃላፊዋ ለምክር ቤቱ አብራርተዋል።

ማምሻውን በተጠናቀቀው የምክር ቤቱ የማጠቃለያ ጉባኤ የከተማ አስተዳደሩን የኦዲት ሪፖርት የቀረበ ሲሆን በሪፖርቱ ዙሪያ ሰፊ ውይይት ተደርጓል ።

Share this Post