በዓለም አቀፍ ደረጃ ለ32ኛ ጊዜ በሀገራችን ለ31 ግዜ የሚከበረውን የአረጋውያን ቀን ምክንያት በማድረግ የአዲስ አበባ ኮሙዩኒኬሽን ቢሮ ሰራተኞችና አመራሮች የወደቁትን አንሱ የነዳያን መርጃ ማህበርን ጎብኝተዋል።
የአዲስ አበባ ኮሙዩኒኬሽን ቢሮ ማህበራዊ ኃላፊነቱን ከመወጣት ረገድ ከሚመለከታቸው አካላት ጋር በቅንጅት በበጎ ፈቃድ አገልግሎት መርሀግብር በክረምትና በበጋ የአረጋውያንና ድጋፍ ለሚሹ ወገኖች የቤት እድሳት ማከናወን ፣ማዕድ ማጋራትና በከተማ ደረጃ የምገባ ማዕከላት አገልግሎትን መደገፍን ጨምሮ በመሰል ማህበራዊ ኃላፊነቶች ላይ የበኩሉን አስተዋጽኦ እያበረከተ ይገኛል።
የቢሮው የቴክኒክ አማካሪ አቶ ተስፋዬ በሪ እንደገለፁት የወደቁትን አንሱ የነዳያን መርጃ ማህበር ያከናውነውን የማዕድ ማጋራት ተግባርን ጨምሮ እንደ ቢሮ ማህበራዊ ኃላፊነትን ለመወጣት ከሌሎች ሁሉ ጋር በንቃት ይሰራል ብለዋል።
ግለሰቦችና ሌሎችም የመንግሥትና የግል ተቋማት አረጋውያንን በመጎብኘት የዜግነት ግዴታን መወጣት ይገባል ተብሏል ።
የወደቁትን አንሱ የነዳያን መርጃ ማህበር መስራች አቶ ስንታየሁ አበጀ ለአገር ቀጣይነት ውትድርናን ጨምሮ በሁሉም መስክ የላቀ አስተዋጽኦ ያበረከቱ አረጋውያንን መደገፍ አገርን የመውደድ ተግባራዊ ማሳያ መሆኑን ገልፀዋል።
ዜጎች አቅም በፈቀደ ሁሉ በዚህ በጎ ተግባር ላይ ተሳትፎ በማድረግ የኛን ማዕከል ጨምሮ በሌሎችም ማዕከላት የሚገኙ አረጋውያንንና ድጋፍ የሚሹ ወገኖችን መደገፍ ይገባል ሲሉ አጽንኦት ሰጥተው ተናግረዋል ።
የወደቁትን አንሱ የነዳያን መርጃ ማህበር ልዩ ልዩ ድጋፍ የሚሹ ከሦስት መቶ በላይ ወገኖችን በመደገፍ ላይ እንደሚገኝ በመርሀ -ግብሩ ላይ ተገልጿል ።